ቴዲ አፍሮ ከእስር ቤት ከወጣ በኋላ ባደረጋቸው ነገሮች አሜሪካ የሚገኘው ታማኝ በየነ እና አንዳንድ ኢትዮጵያዊያን ደስተኛ እንዳልሆነ እየተነገረ ነው፡፡ ቴዲ ከተፈታ በኋላ በቀጥታ ወደ አሜሪካ ሄዶ ኑሮውን እዚያ እንደሚያደርግና መንግስትን ክፉኛ እንደሚተች በእነታማኝ ዘንድ ቢጠበቅም ቴዲ በተቃራኒው አዲስ አበባ በመቆየት እጅግ ደማቅ ኮንሰርት በአዲስ አበባ ስቴዲየም አከናውኗል፡፡ በዝግጅቱና በአንዳንድ ቃለ ምልልሶቹ ላይ የሰጣቸው አስተያየቶችም እንደታሰበው መንግስትን የሚተቹ አልሆኑም፡፡ የኮንሰርቱ አብዛኛው ክፍል በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን መተላለፉም አሜሪካ በሚገኙት እነ ታማኝ ዘንድ ብስጭትን ፈጥሯል፡፡
የቀድሞው የመድረክ አስተዋዋቂ ታማኝ በየነ ሰሞኑን ለአንድ የኢትዮጵያ መፅሄት በሰጠው አስተያየት በቴዲ ወቅታዊ ሁኔታ ግራ እንደተጋባና ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ድምፃዊው ለኮንሰርት ሥራ አሜሪካ ሲሄድ ስለ ጉዳዩ ማብራሪያ እንደሚጠይቀው ገልጿል፡፡ በመፅሄቱ ላይ እንደተነበበው ቴዲ የአውሮፓ ኮንሰርቶቹን ሥራ ውል የተፈራረመው የመንግስት ደጋፊ ከሆነ ሰው ጋር ነው ያሉ አንዳንድ በውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ሰዎች ለዝግጅቱ ቲኬት እንዳይቆርጡ ቅስቀሳ አድርገዋል ተብሏል፡፡ ነገር ግን ቴዲ በፍራንክፈርት ጀርመን ባቀረበው የመጀመሪያ ኮንሰርት ከ1 ሺህ 3 መቶ በላይ ህዝብ ተገኝቶ በደማቅ ሁኔታ መጠናቀቁ ታውቋል፡፡